Tuesday, December 25, 2018

በስመ ፡ አብ ፡ ወወልድ ፡ ወመንፈስ ፡

ቅዱስ ፡ አሐዱ ፡ አምላክ
ወልደ ፡ አብ ፡ በወልደ ፡ አብ ፡ ክፍል ፡

ዐራት

በቅብዓት ፡ የባሕርይ ፡ ልጅ ፡ ሆነ ፡

ማለት ፡ ምን ፡ ማለት ፡ ነው?
============================================
በቅብዓት ፡ የባሕርይ ፡ ልጅ ፡ ሆነ ፡ ማለት ፡ ምሥጢሩ ፡ ምንድን ፡ ነው? ፡ ቢሉ ፤ ወልድ ፡ በሰውነቱ ፡ የባሕርይ ፡ ሕይወቱን ፡ መንፈስ ፡ ቅዱስን ፡ በመላ(ካለ ልክ ) ፡ ተቀብሎ ፡ ከአብ ፡ የባሕርይ ፡ ልደትን ፡ ተወለደ ፡ ማለት ፡ ነው ፡፡ ምነው ፡ ይህስ ፡ ቢሆን ፡ በአብ ፡ ያልተወለደ ፣ በራሱ ፡ ያልተወለደ ፣ ስለምን ፡ በመንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ ተወለደ? ፡ ቢሉ ፤ ይህስ ፡ ወላዲ ፡ በሚመስለው ፡ ሕይወት ፡ ይወልዳል ፡ እንጅ ፡ በማይመስለው ፡ ሕይወት ፡ አይወለድም ፡፡ ለዚህም ፡ ምሣሌ ፡ ያሥረዳል ፤ እንዴት ፡ ያሥረዳል? ፡ ቢሉ ፤ እነሆ ፡ ዛሬ ፡ በደመ ፡ ነፍስ ፡ ሕያዋን ፡ የሆኑ ፡ እንስሳት ፡  ከእንስሳት ፡ ይወለዳ ፤ በነባቢት ፡ ነፍስም ፡ ሕያው ፡ የሆነ ፡ ሰውም ፡ ከሰው ፡ ይወለዳል ፡፡ በደመ ፡ ነፍስ ፡ ሕያው ፡ ያልሆነ ፡ ከእንስሳ ፤ በነባቢት ፡ ነፍስ ፡ ሕያው ፡ ያልሆነ ፡ ከሰው ፡ እንዳይወለድ ፤ እንደዚህም ፡ ሁሉ ፡ መንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ ለአብ ፡ ሕይወቱ ፡ ስለሆነ ፡ በመንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ ሕያው ፡ ያልሆነ ፡ ከአብ ፡ አይወለድምና ፡ በመንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ ሕይወትነት ፡ ከአብ ፡ ተወለደ ፡፡ “ወበከመ ፡ ለአብ ፡ ቦቱ ፡ ሕይወት ፡ ኀቤሁ ፡ ከማሁ ፡ ለወልድኒ ፡ ወሀቦ ፡ ሕይወተ ፡ ከመ ፡ ይኩን ፡ ሕይወት ፡ ኀቤሁ(ለአብ ፡ በራሱ ፡ ሕይወት ፡ እንዳለው ፡ እንዲሁ ፡ ለወልድም ፡ ሕይወት ፡ ይኖረው ፡ ዘንድ ፡ ሕይወትን ፡ ሰጠው ፤ እስመ ፡ ወልደ እግዚአብሔር ፡ ወልደ ፡ እጓለ ፡ እመሕያው ፡ ውእቱ ፡ (የእግዚአብሔር ፡ ልጅ ፡ የሰው ፡ ልጅ ፡ ነውና))” ፡ እንዳለ ፡ ወንጌለ ፡ ዮሐንስ(ምዕ ፡ 5t 26) ፡፡
ወልድ ፡ እምቅድመ ፡ ዓለም ፡ በመለኮቱ ፡ ከአብ ፡ ሲወለድ ፡ በባሕርየ ፡ መለኮት ፡ መቀበል ፡ የለበትምና ፡ መንፈስ ፡ ቅዱስን ፡ ተቀብሎ ፡ ተወለደ ፡ ይሉት ፡ ዘንድ ፡ አይገባም ፤ ዛሬ ፡ ግን ፡ በሥጋ ፡ ርስት(በሥጋነቱ) ፡ መቀበል ፡ አለና ፡ የባሕርይ ፡ ሕይወቱ ፡ መንፈስ ፡ ቅዱስን ፡ ተቀብሎ ፡ ከአብ ተወለደ ፡ ይባላል ፡ እንጅ ፡፡ “መኑ ፡ ውእቱ ፡ ወልዱ ፡ ዘተወፈየ ፡ ኵነኔ ፡ አብ ፡ እንበለ ፡ ሥጋሁ ፡ ወአኮ ፡ መለኮቱ ፤ ወመለኮትሰ ፡ ኢይትወፈይ ፡ ኵነኔ ፡ ወኢይነሥእ ፡ ሥልጣነ ፡ እመለኮት ፤ ወኢይሰይሞ ፡ መለኮት ፡ ለመለኮት (የፍትረትን ፡ ሁሉ ፡ ፍርድ ፡ የተቀበለ ፡ ልጁ ፡ ማን ፡ ነው? ፡ ከሥጋው ፡ መለኮትም ፡ አይደል ፡ መለኮትስ ፡ ፍርድን ፡ አይቀበልም ፡ ሥልጣንንም ፡ ከመለኮት ፡ አይወስድም ፡ መለኮትን ፡ መለኮት ፡ አይሾመውም)” ፡ እንዳሉ ፡ ሊቃውንት ፡ በመዝገበ ፡ ሃይማኖት(አንቀጽ ፡ 1 ፡ ቁ 35-36) ፡፡
እነሆ ፡ ዛሬ ፡ የዚህ ፡ ዓለም ፡ ልጅ ፡ እገሊት ፡ እናትህ ፤ እገሊት ፡ አባትህ ፡ ነው ፡ ካላሉት ፡ አባት ፡ እናቱን ፡ አየውቅም ፡፡ እንደዚህም ፡ ሁሉ ፡ ወልድ ፡ “እግዚአብሔር ፡  ይቤለኒ ፡ ወልድየ ፡ አንተ ፡ ወአነ ፡ ዮም ፡ ወለድኩከ( እግዚአብሔር ፡ አለኝ ፡ አንተ ፡ ልጄ ፡ ነህ ፡ እኔ ፡ ዛሬ ፡ ወለድኩህ)” ፡ ማለቱ ፡ ወልድ ፡ ከአብ ፡ እንደተወለደ ፡ የማያውቅ ፡ ሁኖ ፡ አብ ፡ ነግሮት ፡ ነውን?ቢሉ ፤ እንደዚህስ ፡ አይደለም ፡ ይልቁንም ፡ ለሐዋርያት ፡ ያልጠየቁትን ፡ ምሥጢር ፡ ሲነግራቸው ፡ እንጅ ፡ ነው ፡፡ ማለትም ፡ አብ ፡ ለሐዋርያት ፡ ሲያስተምር ፡ ለወልድ ፡ የነገረ ፡ እየመሰለ ፡ ያስተምራቸዋል ፡፡ ሐዋርያት ፡ ግን ፡ ኋላ ፡ እየጠየቁ ፡ ይረዱታል ፤ ይህም ፡ ይታወቅ ፡ ዘንድ ፡ ዓርብ ፡ ሊሰቀል ፡ በምሴተ ፡ ሐሙስ ፡ “አባ ፡ ቅዱስ ፡ ዕቀቦሙ ፡ በስምከ” ፡ ብሎ ፡ ጸለየላቸው ፡፡ ሐዋርያት ፡ “ዕቀቦሙ” ፡ እየአለ ፡ የሚጸልይልን ፡ ከዚህ ፡ ዓለም ፡ በሞት ፡ ውሰዳቸው ፡ ሲል ፡ ነው ፡ ብለው ፡ ጌታን ፡ ጠረጠሩት ፤ ጌታም ፡ ቢጠረጥሩት ፡ “ወኢይብለከ ፡ ከመ ፡ ትንሥኦሙ ፡ እምዓለም ፡ ዳዕሙ ፡ ከመ ፡ ትዕቀቦሙ ፡ እምእኩይ” ፡ ብሎ ፡ ጸለየላቸው ፡ እኩያን ፡ የተባሉ ፡ አጋንንት ፡ መናፍቃን ፡ ናቸው ፡ “ዕቀቦሙ” ፡ ማለቴም ፡ ከፍትወታተ ፡ እኩያት ፡ ከኃጣውእ ፡ ርኩሳት ፡ ጠብቃቸው ፡ ስልህ ፡ ነው ፡ እንጅ ፡ ከዚህ ፡ ዓለም ፡ በሞት ፡ ውሰዳቸው ፡ ስልህ ፡ አይደለም ፤ ብሎ ፡ ወልድ ፡ ለአብ ፡ የነገረው ፡ መሰለ ፤ ይህንን ፡ ጊዜ ፡ ወልድ ፡ “ዕቀቦሙ” ፡ ብሎ ፡ የጸለየውን ፡ ለሕይወት ፡ እንጅ ፡ ለሞት ፡ እንዳልሆነ ፡ አብ ፡ የማያውቅ ፡ ሆኖ ፡ ወልድ ፡ ነግሮት ፡ አይደለም ፡ ለሐዋርያት ፡ ለማስረዳት ፡ ነው ፡ እንጅ ፡፡ እንደዚህም ፡ ሁሉ ፤ “አንተ ፡  ልጄ ፡ ነህ ፤ ዛሬ ፡ ወድኩህ ፡ አለኝ” ፡ ማለቱ ፤ እምቅድመ ፡ ዓለም ፡ በመለኮቱ ፡ የባሕርይ ፡ ልጅነት ፡ ያለው ፡ ሲሆን ፡ ልጅነትን ፡ ስለሚሻ ፡ ስለ ፡ ሥጋ ፡ እንግድነት ፡ ዛሬ(በጊዜ ፡ ተዋሕዶ)  ፡ በሰውነቱ ፡ ከአብ ፡ የባሕርይ ፡ ልደት ፡ መወለዱን ፡ ሲያጠይቅ ፣ ለሐዋርያት ፡ ሲነግራቸው ፡ እንጅ ፡ የማያውቅ ፡ ሁኖ ፡ አብ ፡ ነግሮት ፡ አይደለም ፡፡

ምስጋና ፡ ለሥሉስ ፡ ቅዱስ
ክብር ፡ ለወለተ ፡ ዳዊት ፡ ወላዲተ ፡ አምላክ ፡ ቅድስት ፡ ድንግል ፡ ማርያም
ክብር ፡ ለመስቀለ ፡ ክርስቶስ ፡ እጸ ፡ መድኃኒት ፡ ኃይልነ ፡ ወጸወንነ፡፡
ይቀጥላል፡፡

No comments:

Post a Comment