Wednesday, December 12, 2018

ወልደ ፡ አብ ፡ በወልደ ፡ አብ ክፍል ፡ አንድ


የጌታችን ፡ የባሕርይ ፡ ልጅነት ፡ እና ፡


የቤተ ፡ አይሁድ ፡ ካሮች ፡ ውድቀት
======================================
ወንድሞች ፡ እህቶች ፡ እንደምን ፡ አላችሁልኝ?ሕይወት ፡ እንዴት ፡ ነው?ሁሉም  ሠላም?አምላክ ፡ ይመሥገን ፡፡ የዛሬው ፡ መልእክቴ ፡ የሚያተኩረው ፡ በቅርቡ ፡ አንዳንድ ፡ ወንድሞች ፡ “እናንተ ፡ ቅብዐቶች ፡ ለመስቀልና ፡ ለጻድቃን ፡ ስግደት ፡ አይገባም ፡ ብላችሁ ፡ ጽፋችኋል ፡ በመጽሐፋችሁ” ፡ እያሉ ፡ ሲከሱን ፡ ሲወቅሱን ፡ አስተውያለሁ ፡፡ የቅብዐቱን ፡ ጣዕመ ፡ ምሥጢር ፡ ሳያውቁት ፡ በልካችን ፡ እያበዙ ፡ አንድ ፡ መንፈስ ፡ ቅዱስን ፡ ሲበዘብዙት ፡ ብንመለከትም ፡ የፍርዱ ፡ ባለቤት ፡ አምላክ ፡ እሱ ፍርዱን ፡ ያስቀምጣል ፡ ፡ ማቴ 12፡ 32 ፤ ብዙ ፡ ወንድሞችና ፡ እህቶችንም ፡ በዚህ ፡ ቃል ፡ ምክንያት ፡ ድጋሚ ፡ አጥምቀው ፡ እስላም ፡ አረሚ ፡ አድርገውበታል ፤ እያደረጉበትም ፡ ይገኛል ፡፡ ስለዚህ ፡ እውነታው ፡ ምን ፡ እንደሆነ ፡ መጻፍ ፡ ስላለብኝ ፡ ከመጽሐፉ ፡ ያለውን ፡ ቃል ፡ ሳልጨምር ፡ ሳልቀንስ ፡ እንዲህ ፡ አርበዋሁ፡፡ አንብብዋ ፡ ለመልእት ፡ እምጥታ ፡ እስከ ተፍጻሜታ ፤ እንዲሉ ፤ ከመጀመሪያው ፡ እስከመጨረሻው ፡ ሳያነቡ ፡ የወደቁት ፡ ካሮች ፡ እኛን ፡ ማላመጥ ፡ አፋቸውን ፡ መፍቻ ፡ ስላደረጉት ፡ ነው ፡ እንጅ ፤ በወልደ ፡ አብ ፡ ላይ ፡ የተገለጠው ፡ ቃል ፡ ለቅዱሳንና ፡ ለመስቀል ፡ ስግደት ፡ አያስፈልግም ፡ የሚል ፡ አይደለም ፡፡ ስለሆነም ፡ የመጽሐፉን ፡ ሙሉ ፡ ኃይለ ፡ ቃል ፡ እንደሚከተለው ፡ ላስነብባሁ፡፡

የጌታችን ፡ የባሕርይ ፡ ልጅቱ ፡ እንዴት ፡ ነው? ፡ እንዲህ ፡ ነው ፡ ተብሎ ፡ ይመረመራልን? ፡ ቢሉ ፡፡ የጌታችን ፡ የባሕርይ ፡ ልደት ፡ ይቅርና ፡ የእኛ ፡ የፀጋ ፡ ልጅነት ፡ እንኳን ፡ አይነገርም ፡ አይመረምርም ፡፡ “ግሩም ፡ ቅድሳቲከ ፡ አቡሁ ፡ ለእግዚእነ ፡ ወመድኃኒነ ፡ ኢየሱስ ፡ ክርስቶስ ፡ ዘውእቱ ፡ ባሕቲቱ ፡ በእንተ ፡ ባሕቲትከ ፡ አቡሁ ፡ በጽድቅ ፡ አንተ ፡ ወኢይትረከብ ፡ ልደቱ ፡ ዘእምኔከ” ፡ እንዳለ ፡ ቄር ፡ ቅዳሴ ፡ t10 ፡፡
የእኛ ፡ የጸጋ ፡ ልጅነታችን ፡ እንዳይመረመር ፡ የአይሁድ ፡ አለቃቸው ፡ ኒቆዲሞስ ፡ የሚባል ፡ የቤተ ፡ አይሑድ ፡  አለቃቸው ፡ ምሁረ ፡ ኦሪት ፡ ነበር ፡ እሱም ፡ የጌታችን ፡ የትምህርቱን ፡ ስፋት ፣ የተአምራቱን ፡ ብዛት ፡ አይቶ ፡ ሌሊት ፡ ሂዶ ፡ ለጌታችን ፡ ሰገደለት ፤ ስለምን ፡ ሌሊት ፡ ሄደ? ፡ ቢሉ ፤ አይሁድ ፡ ክርስቶስ ፡ ካስተማረ ፡ ወዲህ ፡ እኛን ፡ ቆሎ ፡ በስልቻ ፣ ዳቦ ፡ በቅንብቻ ፡ ይዞ ፡ የሚጠይቀን ፡ አጣን ፤ አሁንም ፡ ለእሱ ፡ ሂዶ ፡ የሚሰግድለት ፡ ቤቱ ፡ ይተኮስ ፣ ንብረቱ ፡ ይወረስ ፡ ብለው ፡ ሕግ ፡ ሠርተው ፡ ስለነበር ፡ ስለዚህ ፡ ሌሊት  ፤ ሂዶ ፡ ሰገደለት ፡ ሙሉ ፡ ታሪኩን ፡ ከዮሐ ፡ ወን ፡ ምዕ 3 t 1-8 ፡ ተመልከት ፡፡ “መንፈስ ፡ ኀበ ፡ ዘፈቀደ ፡ ይነፍሕ ፡ ወቃሎ ፡ ትሰምዕ ፡ ወኢተአምር ፡ እምኀበ ፡ ይመጽእ ፡ ወኀበሂ ፡ የሐውር ፡ ወከማሁኬ ፡ ውእቱ ፡ ኩሉ ፡ ዘይትወለድ ፡ እመንፈስ ፡ ቅዱስ”፡ ብሎ ፡ በምሳሌ ፡ ነገረው ፡፡ “መንፈስ ፡ ኀበ ፡ ዘፈቀደ ፡ ይነፍሕ” ፡ ማለቱ ፡ ነፋስ ፡ በፈቀደው ፡ ይነፍሳል ፡ ሲል ፡ ነው ፡፡ ምነዋ ፡ የነፋስ ፡ ምን ፡ ፈቃድ ፡ አለውና ፡ በወደደው ፡ ይነፍሳል ፡ አለ?? ፡ ቢሉ ፤ ቀኝ ፡ ነፈሰ ፣ ግራ ፡ ነፈሰ ፡ ማለት፡ አለና ፡ ስለዚህ ፡ ወደ ፡ ወደደው ፡ ይነፍሳል ፡ አለ ፡፡ “ወቃሎ ፡ ትሰምዕ” ፡ ማለቱ ፡ የነፋስ ፡ ቃሉን ፡ ትሰማዋለህ ፡ ሲል ፡ ነው ፡፡

 የነፋስ ፡ ቃል ፡ ረቂቅ ፡ አይደለምን ፡ እንደምን ፡ ይሰማዋል? ፡ ቢሉ ፤ ዛፉን ፡ ሲአናውጥ ፣ ባሕሩን ፡ ሲገስጽ ፡ በግብሩ ፡ ይሰማልና ፡ ስለዚህ ፡ ቃሉን ፡ ትሰማለህ ፡ አለ ፡፡ “ወኢተአምር ፡ እምኀበ ፡ ይመጽእ ፡ ወኀበሂ ፡ የሐውር” ፡ ማለቱ ፡ ነፋስ ፡ ሲመጣ ፡ ሲሔድ ፡ አታይም ፡ ሲል ፡ ነው ፡፡ ምነዋ ፡ ግራ ፡ ነፈሰ ፣ ቀኝ ፡ ነፈሰ ፡ ይባል ፡ የለምን?ስለምን ፡ አታይም ፡ አለ? ፡ ቢሉ ፤ የነፋሳትን ፡ መውጫ ፡ የነፋሳትን ፡ መግቢያ ፡ አታውቅም ፡ ሲል ፡ ነው ፡፡ “ወከማሁኬ ፡ ውእቱ ፡ ኩሉ ፡ ዘይትወለድ ፡ እመንፈስ ፡ ቅዱስ “ ፡ ማለቱም ፡ ከመንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ የሚወለድ ፡ ሰው ፡ እንደዚህ ፡ ነው ፡ ሲል ፡ ነው ፡፡ ይህ ፡ የሰም ፡ አነጋገር ፡ ነው ፡፡
ወርቁ ፡ ግን ፡ መንፈስ ፡ የተባለ ፡ እግዚአብሔር ፡ መንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ ነው ፡፡ “መንፈስ ፡ ኀበ ፡ ፈቀደ ፡ ይነፍሕ” ፡ ማለቱ ፡ መንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ በወደደው ፡ ሕሊና ፡ ያድራል ፡ ሲል ፡ ነው ፡፡ ምነዋ ፡ መንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ አድልዎ ፡ ምርጫ ፡ አለበትን? ፡ ቢሉ ፤ ሃይማኖት ፡ ተምሮ ፣ ምግባር ፡ ትሩፋት ፡ ሠርቶ ፡ ፣ ንስሐ ፡ ገብቶ ፡ ባገኘው ፡ ልቡና ፡ ያድራል ፡ ሲል ፡ እንጅ ፤ አድልዎ ፡ በመንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ ዘንድ ፡ የለም ፡፡ “ወቃሎ ፡ ትሰምዕ” ፡ ማለቱ ፡ ቃሉን ፡ ትሰማዋለህ ፡ ሲል ፡ ነው ፡፡ ምነዋ ፡ የመንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ ቃል ፡ ረቂቅ ፡ አይደለምን? ፡ ቢሉ ፤ መንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ ያደረበት ፡ ሰው ፡ በደመና ፡ ሲበር ፣ ሕገ ፡ ወንጌልን ፡ ሲአስተምር ፡ ይሰማልና ፡ ስለዚህ ፡ “ወቃሎ ፡ ትሰምዕ” ፡ አለ ፡፡ “ወኢተአምር ፡ እምኀበ ፡ ይመጽእ ፡ ወኀበሂ ፡ የሐውር” ፡ ማለቱ ፡ በሙሴ ፡ የነበረ ፡ መንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ በኢያሱ ፤ በኤልያስ ፡ የነበረ ፡ መንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ በኤልሳዕ ፡ ሲአድር ፡ እንልታየ ፤ መንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ መጥቶ ፡ በሰው ፡ ላይ ፡ ሲአድር ፡ ፣ ከሰው ፡ ሲለይ ፡ አይታይም ፡ ሲል ፡ ነው ፡፡ በዚህ ፡ ካልታወቀ ፡ በምን ፡ ይታወቃል? ፡ ቢሉ፤ ሃይማኖት ፡ በማጽናቱ ፣ ምግባር ፡ በማሠራቱ ፡ ፣ ንሥሐ ፡ በማስገባቱ ፡ ይታወቃል ፡፡ መንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ የተነሣው ፡ ሰው ፡ በምን ፡ ይታወቃል? ቢሉ ፤ ቃለ ፡ ሃይማኖት ፡ ሲነገር ፤ ሰይጣን ፡ በልቡናው ፡ ገብቶ ፡ ቃለ ፡ እግዚአብሔርን ፡ ያስንቀዋል ፣ የሥጋውን ፡ ሥራ ፡ ያሳስበዋል ፣ ነገር ፡ ዘርቅ ፡ ያናግረዋል : “የአትትዎ ፡ ለኃጥእ ፡ ከመ ፡ ኢይርአይ ፡ ስብሐተ ፡ እግዚአብሔር” ፡ እንዳለ ፡ ኢሳይያስ ፡ ምዕ 26 t9 ፡፡
የጌታ ፡ የባሕርይ ፡ ልጅነቱ ፡ እንዲህ ፡ ነው ፡ ተብሎ ፡ ካልተነገረ ፡ የርሱ ፡ የባሕርይ ፡ የእኛ ፡ የጸጋ ፡  መሆኑ ፡ በምን ፡ ይታወቃል? ፡ ቢሉ ፤ በግብሩ ፡ ይታወቃል ፣ መጽሐፍም ፡ ይመሠክራል ፡፡
ሀ. በግብሩ ፡ ይታወቃል ፡ ማለት ፡ እንዴት ፡ ነው?
እኛ ፡ ስንወለድ ፡ አፈማኅፀን ፡ ሳንፈታ ፣ ድንግልና ፡ ሳናፈርስ ፡ መወለድ ፡ አይቻለንም ፤ ጌታችን ፡ ግን ፡ የባሕርይ ፡ ልጅ ፡ ነውና ፡ አፈ ፡ ማኅፀን ፡ ሳይፈታ ፣ ድንግልና ፡ ሳያፈርስ ፡ በድንግልና ፡ ተፀንሶ ፡ በድንግልና ፡ ተፀንሶ ፡ በድንግልና ፡ ተወለደ ፡ ይህ ፡ የባሕርይ ፡ ልጅነቱን ፡ ያጠይቃና ፡ በግብሩ ፡ ይታወቃል ፡ ማለት ፡ ስለዚህ ፡ ነው ፡፡ “ወአማኑኤልሰ ፡ አንቀጸ ፡ ድንግልና ፡ ኢፈትሐ ፡ ከመ ፡ ሰብእ ፡ ወመዛግብተ ፡ ድንግልና ፡ ኢበተከ ፡ እስመ ፡ አምላክ ፡ ውእቱ ፡ ወበከመ ፡ ቦአ ፡ በማኅፀን ፡ ተወልደ ፡ ዘእንበለ ፡ ሙስና ፡ እስመ ፡ ከማሁ ፡ ተፀንሰ ፡ ዘእንበለ ፡ ሙስና ፡ ወመጽአ” ፡ እንዳለ ፡ ተረፈ ፡ ቄርሎስ ፡፡
ለ. መጽሐፍ ፡ እንዴት ፡ ይመሠክራል?
መጽሐፍ ፡ እንዴት ፡ እንዴት ፡ ይመሰክራል? ፡ ቢሉ ፤ ቅዱስ ፡ ጳውሎስ ፡ በዕብ ፡ ምዕ 2t 01 ፡ “ዘቀደሶሙ ፡ ለእሙንቱ ፡ ወእለሂ ፡ ተቀደሱ ፡ ኅቡረ ፡ እም1ዱ (እነሱን ፡ ያከበረና ፡ እሱና ፡ የከበሩ ፡ እነሱ ፡ ካንድ ፡ ከእግዚአብሔር ፣ ከአንድ ፡ ከአብርሃም ፡ ተገኝተዋልና) ፡ ወበእተዝ ፡ ኢየኃፍር ፡ አኃውየ ፡ ብሂሎቶሙ(ስለዚህ ፡ ወንድሞቼ ፡ ማለትን ፡ አያፍርም)” ፤ ብሎ ፡ የተናገረውን ፤ ቅዱስ ፡ ዮሐንስ ፡ አፈወርቅ ፡ “ነጽርኬ ፡ ከመ ፡ ሀሎ ፡ ርኅቀት ፡ ማዕከሌነ ፡ ወማዕከሌሁ ፡ ውእቱ ፡ ወልድ ፡ ዘበአማን ፡ ወንሕነ ፡ ውሉድ ፡ ዘበጸጋ ፡ ውእቱ ፡ ፈጣሪ ፡ ወንሕነ ፡ ፍጡራን ፡ ውእቱ ፡ መድኅን ፡ ወንሕነ ፡ ድኁናን” ፡ ብሎ ፡ ተርጕሞታል ፡፡ “ውእቱ ፡ ወልድ ፡ ዘበአማን” ፡ ማለቱ ፡ የርሱ ፡ ወልድ ፡ መባሉ ፡ የባሕርይ ፡ ነው ፤ እኛ ፡ ውሉድ ፡ መባላችን ፡ የጸጋ ፡ ነው ፡፡ እርሱ ፡ ፈጣሪ ፡ ነው ፤ እኛ ፡ ፍጡራን ፡ ነን ፤ እርሱ ፡ መድኅን ፡ መባሉ ፡ የባሕርይ ፡ እኛ ፡ ድኁናን ፡ መባላችን ፡ የጸጋ ፡ ነው ፡፡ በጸጋ ፡ ልጅነትና ፡ በባሕርይ ፡ ልጅነት ፡ መካከል ፡ ያለውን ፡ ልዩነት ፡ ጠንቅቆ ፡ ማወቅ ፡ ይገባል ፡፡ መጽሐፍ ፡ ይመሰክራል ፡ ማለት ፡ ስለዚህ ፡ ነው ፡፡
ዳግመኛም ፡ እኛ ፡ የጸጋ ፡ ልጆች ፡ 3ት ፡ መዓልት ፡ 3ት ፡ ሌሊት ፡ በከርሠ ፡ መቃብር ፡ አድረን ፡ መነሣት ፡ አይቻለንም ፤ እሱ ፡ ግን ፡ የባሕርይ ፡ ልጅ ፡ ነውና ፡ 3ት ፡ መዓልት ፡ 3ት ፡ ሌሊት ፡ በከርሠ ፡ መቃብር ፡ አድሮ ፡ መግነዝ ፡ ፍቱልኝ ፡ መቃብር ፡ ክፈቱልኝ ፡ ሳይል ፡ ተነሣ ፡ ፤ በግብሩ ፡ ይታወቃል ፡ ማለት ፡ ስለዚህ ፡ ነው ፡፡ “እፎ ፡ ኢኮነ ፡ ወልደ ፡ ዘበአማን ፡ እንዘ ፡ ሰማዕተ ፡ ይከውኖ ፡ ትንሣኤ ፡ ሙታን” ፡ እንዳለ ፡ ቄርሎስ ፡፡ እንዲህ ፡ ማለቱ ፡ ሙቶ ፡ መነሣቱ ፡ የባሕርይ ፡ ለጅነቱን ፡ ያጠይቃል ፡ ማለት ፡ እንዴት ፡ ነው? ፡ አግዝእትነ ፡ ማርያም ፡ አልተነሣችምን? ፡ ልጅነቷ ፡ የጸጋ ፡ አይደለምን? ፡ ቢሉ ፤ የእግዝእትነ ፡ ማርያም ፡ መነሣት ፡ የእሱን ፡ የባሕርይ ፡ ልጅነት ፡ ያጠይቃል ፡፡ እንደምን ፡ ያጠይቃል? ፡ ቢሉ ፤ቅድስት ፡ ድንግል ፡ ማርያም ፡ የባሕርይ ፡ አምላክ ፡ የሆነውን ፡ ስለወለደች ፡ ተነሣች ፡ እንጅ ፤ በጸጋ ፡ ልጅነትማ ፡ የአቡነ ፡ ገብረ ፡ ሕይወት ፣ የአቡነ ፡ ተክለ ፡ ሃይማኖት ፡ እናቶችስ ፡ የጸጋ ፡ ልጆች ፡ አይደሉምን? ፡ ዳሩ ፡ ግን ፡ እነሱ ፡ የወለዱት ፡ የጸጋ ፡ ልጅ ፡ ነውና ፡ አልተነሡም ፡ ገና ፡ ትንሣኤ ፡ ዘጉባዔን ፡ ይጠብቃሉ ፡፡ “እመሰ ፡ ኀደረ ፡ ላዕሌሁ ፡ ቃል ፡ ዘከመ ፡ ኀደረ ፡ ላዕለ ፡ ኩሎሙ ፡ ቅዱሳን ፡ ወእሉ ፡ ኩሎሙ ፡ ቅዱሳን ፡ ሶበ ፡ ሞቱ ፡ ለምንት ፡ ኢተንሥኡ ፡ ዘእንበለ ፡ ዳዕሙ ፡ ዝንቱ ፡ ዘተወልደ ፡ እምእግዝእትነ ፡ ማርያም ፡ ባሕቲቱ ፡ ተንሥአ ፡ እሙታን ፡ አመ ፡ ሣልስት ፡ እለት” ፡ እንዳለ ፡ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ፡፡ እርሷ ፡ ግን ፡ ስለከዊነ ፡ ትስብእት ፡ በቅብዓተ ፡ መንፈስ ፡ ቅዱስ ፡ የባሕርይ ፡ ልጅ ፡ የሆነውን ፡ ወልዳለችና ፡ ሞታ ፡ ተነሣች ፡፡ እመቤታችን ፡ በልጅዋ ፡ ሥልጣን ፡ ተነሣች ፡ እንጅ ፡ በእርሷ ፡ ሥልጣን ፡ አልተነሣችም ፡ “ወአንሣእክዋ ፡ ለወላዲትየ” ፡ እንዳለ ፡፡ ጌታ ፡ ግን ፡ የባሕርይ ፡ አምላክ ፡ ነውና ፡ በገዛ ፡ ሥልጣኑ ፡ ተነሣ ፡፡ “ወተንሣእኩ ፡ በሥልጣነ ፡ ባሕቲትየ (በገዛ ፡ ሥልጣኔ ፡ ተነሣሁ)” ፡ እንዳለ ፡ ቄርሎስ (ሃይ.አበው ፡ ምዕ ፡ 73 ፡ ክ ፡ 12t14) ፡፡
ይቀጥላል

ካሮቹ ፡ የወደቁት ፡ ይህንን ፡ ቃል ፡ ሳያዩ ፡ ቆርጠው ፡ በማንበባቸው ፡ ነው፡፡

No comments:

Post a Comment